አስተውላችሁ ከሆነ፣ በስልክ፣ በእጅ ሰአት ወይም ደግሞ ራሳቸውን የቻሉ ርምጃን የሚቆጥሩ መሳሪያዎችን የሚገለገሉ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ነው፡፡ እርስዎም ተገልጋይ ይሆናሉ፡፡ ነገሩ ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ እንደኔ አመለካካት ስንፈጠር፣ ተንቀሳቅስን ጤናማ መጠነኛ ምግብ ከተመገብን ክምግብና ካለመንቀሳቀስ ጋር ተያይዘው የሚመጡ ለሞት ከሚዳርጉ በሽታዎች እየራቅን እንሄዳለን፡፡
አንግዲህ በመረጃ የተደገፉ ምክሮችን ማካፈል ተገቢ ስለሆነ፣ ርዕሱን በሚመለከት የቀረበ ጥናት ላካፍላችሁ፡፡
ዋናው ነገር በጠንካራ መረጃዎችም የሚታወቀው፣ የሰውነት እንቅስቃሴ አለማድረግና በጣም ውሱን የሆኑ ርምጃዎችን መራመድ ለደም ሥርና የልብ ሕመም ከማጋለጡም በተጨማሪ ባጠቃላይ ለጤና መታወክ ሰበብ ነው፡፡
ነገር ግን፣ መራመድ ካለብን በቂ የሆኑ የርምጃዎች ቁጥር ምን ያህል እንደሆነ ከዚህ በፊት አይታወቅም፡፡ ያም ይህ የማካፍላችሁ ጥናት እስከሚወጣ ድረስ ነው፡፡ European Journal of Preventive Cardiology በተባለ መፅሄት በታተመው ጥናት፣ አጥኝዎቹ ያደረጉት ነገር፣ በቁጥር ምን ያህል ርምጃዎች ከአጠቃላይ ሞት ምክንያቶች በተለይም ከደም ሥርና ልብ ህመም ጋር በተያያዙ ምክንየቶች የመሞት አጋጣሚ ጋር ግንኙነት መኖሩን ማወቅ ፈለጉ፡፡
ያደረጉትን ነገር በአማካይ ለሰባት አመታት ክትትል ያደረጉ የአስራ ሰባት ጥናቶች ውጤቶችን ባንድ ላይ መገምገም ነው፡፡ የጥናቶቹ ተሳታፊዎች ቁጥር 226889 ሲሆን፣ ሰዎች ጤናማ የሆኑና ለደም ሥርና ለልብ በሽታ የመጋለጥ አደጋ ወይም ጠንቅ ያለባቸው ነበሩ፡፡
ጥናቱ እስከ ጁን 2022 ድረስ ባለው ጌዜ ውስጥ የተካተተ ነው፡፡ ወደ ውጤቱ ስንመለስ በየጊዜው በቀን የአንድ ሺ ርምጃዎችን መጨመር፣ በሁሉም አይነት ለሞት በሚዳርጉ ሁኔታዎች መሞትን በአስራ አምስት ከመቶ (15%) የቀነሰው መሆኑን ይገልጣሉ፡፡ በቀን ርምጃዎችን በአምስት መቶ መጨመር እራሱ በደም ሥርና በልብ ህመም ምክንያት መሞትን በሰባት ከመቶ (7%) ይቀንሳል፡፡ በቀን የርምጃዎች ቁጥር በምድብ ተከፋፍሎ ሲታይ፤ ምድብ አንድ በአማካይ በቀን 5537 ርምጃዎች፣ ምድብ ሁለት፣ በቀን በአማካይ 7370 ርምጃዎች፤ ምድብ ሶሰት ደግሞ በቀን በአማካይ 11 529 ርምጃዎች፣ በማንኛውም ጠንቅ የመሞት አደጋዎች የቀነሱ መሆናቸውን ያብራራሉ፡፡ በምድቦች ሲታይ፣ ምድብ አንድ በ48 በመቶ፣ ምድብ ሁለት በ55 በመቶ እናም ምድብ ሶሰት በ76 ከመቶ ነው፡፡ ከላይ እንደተጠቀሰው በየቀኑ የሚራመዱት የርምጃ ቁጥር በጨመረ ቁጥር፣ ጠቀሚታው እየጨመረ ይሄዳል፡፡
በቀን አነስተኛ ርምጃ ተብሎ የተቆጠረው (1594 – 4000 ርምጃዎች) አማካይ 2337 ርምጃዎች እንደማነፃፀሪያ ተወስዶ ከሌሎች ምድቦች ጋር ሲወዳደር፣ በሌላ አመዳደብ ቁጥር አንድ አማካይ 3982 ርምጃዎች፣ ቁጥር ሁለት በቀን አማካይ 6661 ርምጃዎች፣ ቁጥር ሶስት ደግሞ በቀን በአማካይ 10413 ርምጃዎች በቀጥታ በደም ሥርና በልብ ህመም ሰበብ የመሞት አደጋውን፣ ቁጥር አንድ ምድብ በ16% ከመቶ፣ ቁጥር ሁለት ምድብ በ49% ከመቶ፣ ቁጥር ሶስት ምድብ ደግሞ በ77% ከመቶ ይቀንሳሉ፡፡
አጥኝዎቹ ሲያጠቃልሉ፣ በቀን ጠቃሚ የርምጃዎች ቁጥር ከመጠነኛው 3967 (አራት ሺ ሲጠጋጋ) በላይ፣ በደም ሥርና በልብ ህመም ሰበብ ይሁን በሌላ ሰበብ የመሞት አደጋው ይቀንሳል፡፡ ለደም ሥርና የልብ ህመም ሰበብ ደግሞ መጠነኛው መነሻ የርምጃዎች ቁጥር ጠቀሚታ የታየው ከ2337 በላይ ሲሆን ነው፡፡
ከአየር ሀይሎች መዝሙር ትንሽ ለወጥ ብናደርግ፣ ተነሳ ተራመድ ልብህን አበርታ … ርምጃ የሚቆጥሩ መሣሪያዎች በያይነቱ አሉ፣ በአማዞን ዋጋቸው መጠነኛ የሆኑ ርምጀዎን የሚቆጥሩ በኪስ ውስጥ የሚያዙ ወይም ባንገት የሚንጠለጠሉ ወይም ቀበቶ ወይም ሱሪ ላይ ሻጥ የሚደረጉ አሉ፡፡ እኔ የግሌን የምመከረው ከሌላ ዳታ ቤዝ ጋር ከተያያዙ አፖች ይልቅ እንዚህ ከምንም ሌላ ፕሮገ ፀራም ጋር ያልተያያዙትን መጠቀም ይበጃል፡፡ ለምንድነው የማላውቀው ሰው የኔን ርምጃና ሌላም መረጃ የሚሰበስበው? ለማንኛውም በየቀኑ የሚየሄዱትን የርምጃ ቁጥር ከሚችሉ ከመጠነኛ ቁጥር ተነስተው፣ መጨመር ሲፈልጉ ግን መዳረሻውን በአንድ ሺ ርምጀዎች መጨመር ከፍተኛ ጠቀሚታ አለው፡፡
በነገራችን ላይ እንደዚህ አይነት እንቅስቃሴዎች ለአካል ጤንነት ብቻ ሳይሆኑ ለአእምሮ ጤንነትም ይረዳሉ፡፡ በዕድሜ ምክንያት ሊከሰት የሚችለውን የመዘንጋት ወይም የመርሳት ሁኔታን ያዘገያሉ፡፡ ይህ በጥናት የተደገፈ ውጤት ነው፡፡ ከፕሮፌሰር ዮናስ ገዳ ጋር የተደረገውን ውይይት በድረ ገፁ ይመልከቱ፡፡
መንቀሳቀስ ለጤንነት ይበጃል፣ እንኳን ለጤንነት ላገርም ይበጃል፡፡
መልካም ንባብ (አካፍሉ)
ዕድሜ እየገፋ ሲሄድ ከሚከተሉት የጤና ቀውሶች አንዱ የኩላሊት በሽታ ነው፡፡ ይህንን የኩላሊት በሽታ ከፋ ደረጃ እንዳይሻገር የሚደረጉ ነገሮች አሉ፡፡ በአብዛኛው፣ አስካሁን ድረስ የሚደረገው፣ ለኩላሊት በሽታ ጠንቅ የሆኑትን የደም ግፊትና የሰኳር በሽታን በመድሀኒት አማካኝነት መቆጣጠር ነው፡፡ ይህ ግን በራሱ፣ እነዚህ በዕደሜ የገፉ ሰዎችን ከሚገባው በላይ ብዛት ያላቸው መድሐኒቶች እንዲወስዱ፣ አንዳንዴም በመድሐኒቶች ምክንያት ጉዳቶች አንዲከሰቱ ነው ያደረገው፡፡ ጥያቄው ታዲያ፣ መድሐኒት ከመስጠት ውጭ ሌላ ምን አይነት ፕሮገራም፣ የኩላሊት በሸታን ወደከፋ ደረጃ ከመድረስ የሚቀነስ ነገር አለ ወይ ነው፡፡
ጃማ በሚባል የህክምና መፅሄት በቅርቡ የወጣ የምርምር ወይም የጥናት ውጤት ለዚህ ጥያቄ መልስ ይሠጣል፡፡ እኔም የዘገየሁትን ያህል ይህን የጥናት ውጤት ስመለከት፣ በጉጉት ለህብረተሰቡ ለማካፈል ይህን ፅሁፍ አቅርቤያለሁ፡፡ መነበብ ይገባዋል የሚል እምነትም አለኝ፡፡
ሰለኩላሊት በሽታ በጥቂቱ ለመግለፅ፣ ዕድሜያቸው ከ70 አመታት በላይ በሆኑ ሰዎች ከአንድ ሶስተኛ በላይ በሆኑት የኩላሊት በሽታ ይገኝባቸዋል ወይም የታይባቸዋል፡፡ ይህ ሥር የሰደደ የኩላሊት በሽታው ሲለካ የኩላሊት የማጣራት ችሎታው ከ60 በታች ነው፡፡ ጤናማው ቁጥር አንግዲህ ነው፡፡ ችግሩ ምንድን ነው፡፡ የኩላሊት በሸታ ለብዙ በሽታዎች መከሰት ሰበብ ወይም ምክንያት መሆኑ ነው፡፡ በመጠኑ በዝርዝር ለማየት፣ የኩላሊት በሽታ የሚሰከትላቸው ጉዳቶችየሚከተሉት ናቸው፤ የልብና የደም ሥር በሸታዎች፣ የሰውነት አቅም መድከም፣ መውደቅ፣ ተከትሎ ስብራቶች፣ የአእምሮ የማሰብ ወይም የአውቀት ችሎታ መቀነስ፣ በህመም ምክንያት ወደ ሆሰፒታል መግባትና፣ ከዛም ለህይወት ማለፍ ምክንያት መሆን ነው፡፡ ባጠቃላይ ለከባድ ህመምና ለሞት ይዳርጋል፡፡
በቀረበው ጥናት፣ መጠነኛ የሰውነት እንቅስቃሴና የአካል አንቅስቃሴ ማድረግ ጤንነት ላይ የሚያሰከትለውን ውጤት ግምገማ ነው የምንመለከተው፡፡ ጥናቱ ያተኮረው ዕድሜያቸው ከ70 እሰክ 89 በሆኑ ሰዎች ሲሆን፣ አነዚህ ሰዎች፣ ወንድም ሆነ ሴቶች በቂ የሰውነት እንቅስቃሴ የማያደርጉ ማለትም በቀን ከሀያ ደቂቃ በታች ወይም በሳምንት ከ125 ደቂቃዎች በታች የሰውነት ወይም የአካል እንቅስቃሴ የሚያደረጉ ባጠቃላይ መቀመጥ የሚያዘወትሩ ሰዎች ሲሆኑ በተጨማሪም፣ ለሰውነት መድከምና የዕለት ከለት ሥራ ወይም የኑሮ እንቅስቃሴ ማድረግ ሊሳናቸው የሚችሉና ሌሎችም መመዘኛዎችን ጨምሮ የጥናቱ ተሳታፊዎች እንዲሆኑ ተደረገ፡፡
እነዚህ ሰዎች ከሀለት ወገን ተከፍለው አንደኛው ወገን በተዘጋጀው የሰውነት እንቅስቃሴ ፕሮገራም ታሳተፊ ያልሆኑ ሲሆን፣ ሌሎቹ ግን በሚከተለው መንገድ የሰውነት እንቅስቃሴ እንዲያደርጉ ተደርጎ ክትትል በማድረግ ውጤቱን ለመገምገም ነው፡፡ ፕሮገራሙ ሁለት አይነት ሲሆን፣ የመጀመሪያው ጠቅላላ የሰውነት እንቅስቃሴ ግቡም በየቀኑ በመራመድ ባጠቃላይ በሳምንት ውስት የ150 ደቂቃዎች መራመድ፣ ማለትም በየቀኑ ለ30 ደቂቃዎች መራመድ ነው፡፡ ሁለተኛው ክፍል ደግሞ፣ የሰውነት ጥንካሬ፣ የሰውነት ሚዛን መጠበቅና የሰውነት መተጣጠፍ ለመጨመር የሚደረግ የአካል እንቅስቃሴ አንዲለማመዱና ቀጥሎም እንዲያዘወትሩ ማድረግ ነው፡፡ ለዚህኛውም ቀስ ብሎ በመጀመር ግቡ፣ በቀን የአስር ደቂቃዎች ከወገብ በታች የሰውነት ክፍልን የሚያጠነክሩ እና ለአስር ደቂቃዎች የሰውነት ሚዛን መጠበቅ የሚያስችሉ እንቀስቃሴዎችን ማድረግ ነው፡፡ ሰዎቹ የሚጠበቅባቸው በየቀኑ ርምጃዎችና ቀደም ብለው የተጠቀሱትን የአካል አንቅስቃሴዎች በጥምር እንዲያደርጉ ነው፡፡
ክትትሉ ሰዎቹ የሚያደርጉትን የሰውነትና የአካል እንቅስቃሴ መለካት በሚቻልበት ሁኔታ ፕሮገራሙ ሲጀመር ከዚያም በ12ኘው ወር፣ በ24ኘው ወይም በሁለት አመት መረጃዎችን በመሰብሰብ የታየውን ውጤት በስሌት ማየት ነው፡፡ እነዚህ መረጃዎች ሲበሰቡ በተጓዳኛም የኩላሊት የማጣረት ቸሎታን አብሮ ተለክቷል፡፡
ዝርዝር የጥናቱን አሰራር ወይም የተጠቀሙትን ዘዴ አልፍን ውጤቱ ላይ ስናተኩር፤ ከጠቅላለው 1635 የጥናቱ ተሳታፊዎቸ 1199 የሚሆኑት የኩላሊት ማጣራት ችሎታን ለማጥናት ናሙናዎች ሠጥተዋል፡፡ ከነዚህ መሀል አማካይ ዕድሜ 78.9 አመት ሲሆን፣ 66.7% ሴቶች ናቸው፡፡ ጥናቱ ሲጀመር የኩላሊት በሽታ እንዲባባስ ሊያደርጉ የሚችሉ ጠንቆች የስኳር በሽታ በ27.3% ሰዎች፣ የደም ግፊት በ855 ሰዎች፣ የልብና የደም ሥር በሽታ በ354 ሰዎች የነበራቸው ሲሆን፣ ሲጀመር የኩላሊት የማጣራት ችሎታው መጠን ከ60 በታች በ796 ሰዎች ላይ የታየ ነው፡፡
የጥናቱን ውጤት ቁጥር በዝርዝር ሳናስቀምጥ የታየው ውጤት፣ የሰውነት እንቅስቃሴና የአካል እንቅስቀሴ እንዲያደርጉ በተመደቡት ወገን፣ ከሌሎች ጋር ሲወዳደር እየከፋ የሚሄደው የኩላሊት የመድከም ሁኔታ ያዘገመ ወይም የቀነሰ ሆኖ ነው የተገኘው፡፡ የጥናቱ ባለቤቶች ደግመው የሚገልፁት ነገር፣ የአካል አንቅስቃሴ በሚያደርጉት ሰዎች፣ የእንቅስቃሴው መጠን በጨመረ ቁጥር፣ በየጊዜው የሚከሰተው የኩላሊት የመድከም ሁኔታ በጣም ያዘገመ ሆኖ ነው የተገኘው፡፡ ማለትም የከፋ የኩላሊት በሽታ በፍጥነት ከመከሰት መከላከል ተችሏል፡፡
በማጠቃለያቸው የሚነግሩን ነገር፤ በጥናቱ በታየው ውጤት መሠረት፣ የሰውነት እንቅስቃሴ መጠነኛም ቢሆን የኩላሊት የከፋ ሁኔታ ደረጃን መድረስ የማዘግየት ጥቅም ሰላለው፣ የሰውነትና የአካል እንቅስቃሴ እንደመደበኛ ህክምና ለሰዎች መታዘዝ እንዲኖርበት ነው የሚመክሩት፡፡
እንግዲህ እንዲህ አይነት ከመድሐኒት ውጭ በተፈጥሮ የሰውነት እንቅስቃሴ የኩላሊት በሸታን ማዘግየት ከተቻለ፣ በዚህ ዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ሰዎችን ወይመ የቤተሰብ አባላትን፣ በየቀኑ እንቅስቃሴ እንዲያደርጉ፣ ማለትም በቀን ለ30 ደቂቃዎች በአካባቢያቸው እንዲራመዱ፣ በተጨማሪም የታችኛው የሰውነት ክፍልን፣ እግርና ጭን የሚያጠነክር፣ ሚዛን መጠበቅ የሚያስችል የአካል እንቅስቃሴ እንዲያደርጉ ማበረታት ያስፈልጋል፡፡ ከዚህ ጥናት ጋር ያልተያያዘ በተለየም ርምጃዎች በሚያደርጉበት ጊዜ ፈጠን ያሉ ርምጃዎች ማድረግ የጠቅላላ የሰውነት ጥንካሬን እንደሚጨምሩ ቢታወቅም ይሀንን ጠቀሚታ ሁሉም ሰው ይገነዘባል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ማስተዋል ያለብን ነገር ግን፣ ወደተፈለገው ግብ ለመድረስ ቀስ በቀስ እንዲሆን አንጂ ባንድ ጊዜ የታሰበውን እንቅስቃሴ እንዲያደርጉ ከመገፋፋት መቆጠብ እንዳለብን ነው፡፡
መልካም ንባብ፡፡
በቅርቡ ከአሪዞና ኢትዮጵያውያን ማህበረሰብ ጋር ኮቪድን በሚመለከት ውይይት ስናደርግ፣ ለተጠየቁ ጥያቄዎች መልስ ስሠጥ፣ በቂ አንቅልፍ መተኛት ለጤንነት ብሎም የሰውነት መከላከያ አቅምን ለማጠናከር ጥሩ ነው ብዬ ነበር፡፡ ያ አንግዲህ በቂ እንቅልፍ ካለማገኘት ጋር በተያያዘ ሊደረሱ የሚችሉ የሚታወቁ የጤና ችግሮችንና በማስታወስና የሰውነት የበሽታ የመከላከል አቅምም በእንቅልፍ ማነስ ደካማ ሊሆን እንደሚችል የሚታወቁ መረጃዎችን በማገናዘብ ነው፡፡
ሆኖም ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት፣ ከኮቪድ 19 ጋርም ግንኙነት ያለው ሁኔታ ይኖር ይሆነ ብዪ ክትትል ቀጠልኩ፡፡ “የሚገርም ነው!” ይላል ሶሰት አመት የሞላው የእህታችን ልጅ፡፡
American Academy of Sleep Medicine (AASM) የሚባል የባለሙያተኞች ማህበር ይህንን በሚመለከት ያወጣወን መካሪ ሀሳብ አየሁኝና እንደተለመደው ለናንተም ላካፍል ብዬ ወሰንኩ፡፡ በነገራችን ላይ፣ እንቅልፍ ከተነሳ፣ አሜሪካውያን ከሚገባው በላይ ደፋሮች ናቸው ይባላል፡፡ ያለ በቂ እንቅልፍ መኖር፣ ማለትም ቡናም ሆነ ሌሎችን አነቃቂ መጠጦች በመውሰድ በጣም መጠነኛ እንቅልፍ ሥራቸውን ያከናውናሉ፡፡ ወፍ እንደ አገሩ ይጮሃል አንደሚባለው፣ እኛም ነገሩን እንደ ጥሩ አርኣያ ወስደን እንቅልፉን ናቅ አድገን እንውተረተራለን፡፡ አደጋ አለው፡፡
ወደ ምክሩ ልመልሳችሁ፡፡ ከዛ በፊት ግን በጥናት የወጡ ሌሎች መረጃዎችን አንድ ሁለት ልበል፡፡ በ2020 የወጣ ጥናት የሚጠቁመው፣ የኢንፍሉዌንዛ ክትባት ከመወስዳቸው በፊት ለሁለት ቀናት በቂ እንቅልፍ ያገኙ ሰዎች ለክትባቱ ጥሩ ምላሽ አሳይተዋል የሚል ነው፡፡ በሌላ ተመሳሳይ ጥናት ደግሞ አንደዚሁ ከክትባቱ በፊት በቂ እንቅልፍ የነበራቸው ሰዎች ለሄፓታይትስ ኤና ሄፓታይትስ ቢ ክትባት ጥሩ ምላሽ አሳይተዋል የሚል መረጃ አለ፡፡
ለምን ወይም እንዴት ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው፡፡ ባጠቃላይ፣ እንቅልፍ በሚወሰድን ጊዜ፣ ሰውነታቸውን በቀን ከነበረው ውሎ ማረፍ ብቻ ሳይሆን፣ ለሚቀጥለው ቀን ዝግጅትም ለማድረግ ብዙ ሥራዎችን የሚሠራበት ጊዜ ነው፡፡ በመጀመሪያ ሲሰሩ የዋሉ ጡንቻዎችን ማደስ፣ የተጎዱ ሴሎችና የሰውነት ክፍሎችን መጠገን የሚደረገው በእንቅልፍ ጊዜ ነው፡፡ ከዛ ቀጥሎ ደግሞ በሆርሞኖች አማካኝነት፣ የመከላከያ አቅምን ማጎልበትና ማደስ፣ የተለያዩ፣ ሜታቦሊክ ይባላሉ፣ ሁኔታዎች ማስተካክልም ያደርጋል፡፡ አንጎል ደግሞ በተራው፣ በምንተኛበት ጊዜ፣ አዳዲስ ያገኛቸውን መረጃዎች በየቦታው በማስቀመጥ ለሚቀጥለው ቀን ዝግጁ ያደርገናል፡፡ እንደ ባለሙያተኞቹ ገለፃ አዳዲስ መረጃዎችን በየቦታው በማስቀመጥ የአዕምሮ ስሜታችን የተረጋጋ እንዲሆን በማድረግ እንደገናም ለሚቀጥለው ቀን ዝግጁ ያደርገናል፡፡ ይህን ሁኔታ ለመገንዘብ በቂ በየቀኑ የምናያቸው ነገሮች አሉ፡፡ በቂ እንቅልፍ ያልተኛ ሰው ጋር ውይይትም ማድረግ ይከብዳል፤ አንዳንዶች ቀጥታ ወደንጭንጭ እንደሚሄዱም እናውቃለን፡፡ ይህ የሚያሳየው በሀያ አራት ሰአት ውስጥ የሚገባንን የእንቅልፍ ድርሻ እንደምንም ብለን ማግኘት እንደሚኖርብን ነው፡፡ አለዚያ ሰውነታችን በውስጥ በኩል ለተሀድሶና ለጥገና ጊዜ አያገኝም፡፡ ይህን ነገር ሰው ሠራሽ በሆነው በመኪና እንኳን ብንመለከት፣ መኪናውን ለረዥም ጊዜ አቆመዋለሁና ያለማቋረጥ ለረዥም ጊዜ ላሽከርክረው የሚል ያለ አይመስለኝም፡፡ መኪናው በየተወሰነ ሰኣት መቆምና መብረድም ይኖርበታል፡፡
አሁን በዚህ በወረርሽኙ ጊዜ የታየ ነገር ቢኖር ብዙ ሰዎች በቂ እንቅልፍ የማያገኙ መሆናቸው ነው፡፡ በኮምፒውተር ወይም በስልኮቻችን ቤታችን ሆነን ስብሰባና ሥራዎችን ማካሄድ መቻላችን ደግሞ እንቅልፍን መናቅ ወይም ችላ ወደ ማለቱ አድርረሶናል፡፡ ከላይ የጠቀስኩት የባለመያተኞች ማህበር ይህንን በሚመለከት ባደረገው ሰፋ ያለ መጠየቅን የተመረኮዘ ጥናት፣ ከተጠየቁት ሰዎች 33% የሚሆነት በቂና ጤናማ የሆነ የእንቅልፍ ሁኔታ የተዛባባቸው መሆኑን፣ 30% የሚሆኑት ደግሞ በሰኣቱ እንቅልፍ ሊወስዳቸው ያልቻለ መሆኑን ሲመልሱ 29% የሚሆኑት ደግሞ በማታ የሚተኙት የዕንቅልፍ ጊዜ መጠን ላይ ለውጥ ያለ መሆኑን መልሰዋል፡፡
በቂ እንቅልፍን በሚመለከት፣ የባለሙያተኞቹ ማህበር የሚመክረው አብዛኞች ሰዎቸ በየቀኑ ሰባት ሰአታት መተኛት አለባቸው ነው፡፡ በየቀኑ የሚለውን ማስመር አስፈላጊ ነው፡፡ ብዙዎቻችሁ ይቀልዳል እንዴ ሳትሉ አትቀሩም፡፡ ሰባት ሰአት ከየት ይመጣልም ሳትሉ አትቀሩም፡፡ ዋናው ነገር፣ ከሚቀጥለው ቀን መበደር ክልክል ነው፡፡ ሰባት ሰአት እንቅልፍ ለአብዛኛቹ አዋቂ ሰዎች የሚሆን ምክር ነው፡፡
አሁን የኮቪድ ክትባት በስፋት ለህብረተሰቡ እንዲዳረስ ጥረት እየተደረገ ነው (በአሜሪካ)፡፡ በኢትዮጵያም ቢሆን፣ ባለሞያተኞቹ ከፍተኛ ጥረትና ዝግጅት እያደረጉ ነው፡፡ ትልቁ ማነቆ በቂ ምርት አለመኖሩ ሲሆን፣ በቂ ምርት ሲኖር ደግም ያው ሁላችንም የምናውቀው የኢኮኖሚ አቅም ወሳኝ ሊሆን ነው፡፡ ግን እዚህ ላይ፣ አጋጣሚው ቢፈጠር እንደተለመደው ሰብሰብ ብለን ክትባቶች ለኢትዮጵያውን እንዲዳረስ በመጠኑም ቢሆን አስተዋፅኦ ማድረግ የምንችል ይመሰለኛል፡፡
በአሜሪካ አሁን ክትባትና የክትባት አሠጣጥ በየስቴቶቹ መንግሥታት በኩል ሰለነበር፣ ያም እንደምናወቀው ችግርም ሰላለበት፣ በአሜሪካ አዲሱ ሳይንስ የሚያከብረው አስተዳደር፣ ክትባቱ በቀጥታ ወደጤና ተቋማት እንዲደርሰ በማድረግ ክትባት ማግኘት የሚገባቸው ሰዎች አንዲያገኙ ለማድረግ እየሞከረ ነው፡፡ እዚህ ላይ፣ አዳዲስ በሚከሰቱ የቫይረሱ ዝርያዎች ጋር ተያይዞ የሚነሳውን ችግር በማስተዋል፣ ክትባቱ ቶሎ ተዳርሶ፣ ከሌሎች የበሽታው ሥርጭት መከላከያ ተግባራት ጋር በመተጋገዝ የቫይረሱን በስፋት መሠራጨት ማቆም ተገቢ ነው፡፡ ቫይረሱ ካልተሠራጨና ካልተራባ አዲስ ዝርያ የለም፡፡ ይህን ሁሉም ማወቅ አለበት፡፡
ታዲያ የኮቪድ-19 ክትባት ከመውሰድዎ ከአንድ ቀን በፊት በቂ እንቅልፍ መተኛት ክትባቱን ከወሰዱ በኃላም እንዲሁ ለአንድ ቀን በቂ እንቅልፍ መተኛት፣ የሰውንት የመከላከያ አቅምዎን ስለሚያጎለብተው ለክትባቱ ጥሩ ምላሽ ይኖረዎታል ይላሉ ባለሙያተኞቹ፡፡ ይህ ምክር ከመሥመር የወጣም አይደለምና ሁላቸንም በፅሞና ልንቀበለውና ተግባራዊ ልናደረገው ይገባል፡፡
ባጠቃላይ ግን፣ በቂ እንቅልፍ አለማግኘት በሰውነት ላይ የሚያደርሰው ጉዳት ዝርዝ ሰፋ ያለ ነው፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ የሰውነት ግዝፈት ወይም ከመጠን በላይ ክብደት ያላቸው ሰዎች አልጋ ላይ ጋደም ቢሉም በቂ እንቅልፍ የማያገኙበት ሁኔታ አለ፡፡ በእንግሊዝኛ Sleep apnea ይባላል፡፡ ትንፋሻቸው እየተቆራረጠ በቂ ኦከስጅን ወደ ሰውነታቸው ሰለማይደርስ ከፍተኛ ጉዳት ይደርስባቸዋል፡፡ በዚህ ሁኔታ ያገራችን ልጆች ጨምሮ ብዙ ባለሙያተኞች ምርመራ፣ ህክምናና ርዳታ የሚያደርጉም አሉ፡፡ ለወደፊት ትምህርቱን በቀጥታ ከነሱ ማግኝት አንችላለን፡፡ እስከዛ ደረስ ግን ምክሩን አስተውሉም አካፍሉም፡፡ በቂ እንቅልፍ ማግኘትን መናቅ የለብንም፡፡
መረጃ፡ Temporal Links Between Self-Reported Sleep and Antibody Responses to the Influenza Vaccine, International Journal of Behavioral Medicine (2020)
ጎሽ የጤና ትምህርትና ምክር በአማርኛ
አዘጋጅና አቅራቢ ዶ/ር ገበየሁ ተፈሪ
Community health
education in Amharic